አንድ ሰውዬ ሁልጊዜ ወደ ቡና ቤት ጎራ ሲል አንድ ዓይነት መጠጥ በሶት የተለያዩ ብርጭቆዎች በማዘዝ ፊት ለፊቱ ደርድሮ በየተራ ከሶስቱም እየተጎነጬ ነው የሚጠጣው፡፡ ታዲያ ይህ ከሰው ለየት ያለ ባህሪው የሚያስገርመው የመጠጥ ቤቱ አስተናጋጅ አንድ ቀን “ይቅርታ ወንድሜ! ሁልጊዜ አንድ ዓይነት መጠጥ በሶስት ብርጭቆ እያዘዝከኝ ሁሉንም የምትጠጣው ግን አንተው ነህ፤ ከዚህ ሁሉ አንዱን ጠጥተህ ስትጨርስ ሌላውን ባመጣልህ አይሻልም?” ሲል ይጠይቀዋል፡፡
ሰውዬውም “የለም! የለም! አየህ ይህ ትልቅ ምክንያት አለው፤ አንዱ ብርጭቆ የኔ ድርሻ ሲሆን፤ ሁለቱ ግን ለስራ ፊልድ የሄዱ በጣም የምወዳቸው ጓደኞቼ ድርሻ ነው፡፡ ስለዚህ እነሱን ለማስታወስ ስል ነው በሶስት ብርጭቆ አዝዤ የምጠጣው” ሲል ይመልስለታል፡፡
ታዲያ አንድ ቀን ይህ ሰውዬ ያለወትሮው ሁለት ብርጭቆ መጠጥ ብቻ ቢያዘው አስተናጋጁ ግራ በመጋባት “ውይ ዛሬ ምነው ሁለት ብቻ አዘዝከኝ? አንዱ ጓደኛህ ሞተ እንዴ?” ሲል ይጠይቀዋል፡፡
ሰውዬውም “የለም የለም ሁለቱም ደህና ናቸው፤ እኔ መጠጥ ስላቆምኩ የራሴን ድርሻ ቀንሼ ነው” ብሎት እርፍ!!