በሳውዲ አረቢያ የሚገኙ ህገ-ወጥ የተባሉ እህት ወንድሞቻችን ከሃገር ውጡ ተብለው ወደ እናት ሃገራቸው መመለስ ከጀመሩ ሰነባብተዋል፡፡ የድሮው አውሮፕላን ማረፊያ ጉምሩክ ተብሎ የሚጠራው አካባቢ በሰው ብዛት ተጥለቅልቋል፡፡ ለካ ሳውዲ አረቢያን ክልል 15 አድርገናት ነበር፡፡ አይ ይህች እንጀራ፤ ያልፍልናል ብለው ሄደው በግፍ የተባረሩ ወገኖቻችን ናቸው፡፡ በሳውዲ ብዙ ዘመናት ቢያስቆጥሩም የመኖሪያ ፈቃድ የሌላቸው ወገኖች ሶስት እና አራት ልጆች ወልደው መቀመጣቸው ግን ገርሞኛል፡፡ በጣም ያሳዝናል ህፃናት ልጆች ይዘው የሚመጡት እኮ ብዙ ናቸው፡፡ ፈቃድ ሳይኖራቸው እንዴት ነው ወልደው ልጅ የሚያሰቃዩት? እርግጥ ነው ይህን ያህል ዓመታት ሲቆዩ የተፈጥሮ ጉዳይ ነው፤ ለምን ተዋለዱ ብዬ አልጠይቅም፡፡ ግን የሰው ሃገር ውስጥ ሲኖር ከኋላ ለሚመጡት ፍጥረቶች ደህንነት ኃላፊነት መውሰድ ያስፈልጋል፡፡ ምክንያቱም እዛ የታሰሩበት ቦታ ሁሉ የሚበላ የሚቀመስ ሲያጡ ያማቸዋል፤ ከዛ የከፋም ነገር ሊፈጠር ይችላል፡፡ በእርግጥ ድንገተኛ ዱብ እዳ ስለሆነ ከሆነ በኋላ ነው ችግሩ የተከሰተው፡፡
እኔን ግን ከዚህ የበለጠ ግርም ያለኝ ነገር ባዕዳን አባረዋቸው ሃገር አለን ብለው በገዛ ሃገራቸው እዚሁ የሚያርፉበት ድንኳን አካባቢ ኢትዮጵያውያን ነን የሚሉ ወገኖች ከ30 ብር በማይበልጥ ዋጋ የሚሸጠውን ሲም ካርድ በ60 ብር ሲቸበችቡላቸው ነበር፡፡ እኛ ራስ በራሳችን ካልተዛዘንን የሌላ ሃገር ሰው እንዴት ነው የሚያዝንልን? እናም የድሮው መተሳሰባችን ይቀጥል እላለሁ፡፡