Monday, January 28, 2013

የኤሌክትሮኒክስ ቀረጥ እና መዘዙ


ለመጀመር ለጠቅላላ እውቀታችሁ ያህል የላፕቶፕ ዋጋን አነሳለሁ፡፡ ትንሽ ተብሎ የሚጠራው ዋጋ 12 ሺህ ብር ነው፡፡ ታዲያ በዚህ መልኩ አድርጎ የቴክኖሎጂ ርቀት እንዴት ይመጣል እንዲያውም ድቀት እንጂ፡፡ በአሁኑ ወቅት እንደሚታዬው አንዲት ሀገር ለማደግና ለመበልፀግ በሃይ-ቴክ ፋሲሊቲዎች፣ ሶፍትዎሮችና በተለያዩ ቴክኖሎጂዎች መታገዝ አለባት፡፡ ይህ የሚሆነው ዝም ብሎ አይደለም፡፡ የኮምፒዩተር ዋጋ እንደዚህ በተሰቀለበት ጊዜ እንዴት ተብሎ ነው ስለ ብልፅና የሚታሰበው፡፡ ከትንሹ እንጀምር የወረቀት ስራ ለመስራት እንኳን ኮምፒዩተር ቤት ሄደን ነው የምናፅፈው፤ የፈለገ ምስጢር እንኳን ቢሆን፡፡ ይህ ለምን ይሆናል? ኮምፒዩተር ይዘው የምናያቸው ቀበጥ የሀብታም ልጆች ናቸው፡፡ በእርግጥ ከሀብታም ልጆች በጣም ጎበዞች አሉ፡፡ ዓላማቸውን ተረድተው ግብ ለመምታት የሚጥሩ፡፡ አብዛኛዎቹ ግን ሙዚቃ ከመስማትና ፊልም ከመጫንና ከማውረድ ውጪ ምንም ሲያደርጉበት አይታይም፡፡ በጣም የሚገርመው ደግሞ በተለይ በመንግስት መስሪያ ቤቶች ውስጥ ላፕቶፕ መያዝ የስልጣን ደረጃን ለመግለፅ የተቀመጠ መስፈርት ይመስል ምንም ዓይነት መሰረታዊ የኮምፒዩተር እውቀት የሌላቸው ባለስልጣናት ባዶ ኮምፒዩተር ሲዞሩ ማየት የተለመደ ነው፡፡ እና ምን ለማለት ፈልጌ ነው፡፡ ዋጋው ተመጣጣኝ ቢሆንና በእያንዳንዱ ሰው ቤት ውስጥ ቢገባ ከቴክኖሎጂ ጋር የተያያዙ የፈጠራ ስራዎቸ እርግጠኛ ሆኜ የምነግራችሁ ቢያንስ አሁን ካሉበት ከ200 ፐርሰንት በላይ ይጨምራሉ፡፡ ይህም የሚሆነው እንዴት ነው? የመንግስት የቤት ስራ ነው፡፡ በኤሌክትሮኒክስ ላይ በተለይም በኮምፒዩተሮች ላይ የጣለውን እጥፍ የግብር ክፍያ ማንሳት ወይም መቀነስ አለበት፡፡ ይህ ካልሆነ ግን ይህች ሀገር ብዙ እርምጃ ወደፊት አትሸጋገርም፡፡ ለምሳሌ ልማታዊ ባለሀብቶች ናቸው ለሚባሉ ባለሀብቶች ግን ልማታዊ ላልሆኑ ከቀረጥ ነፃ ተፈቅዶላቸው ያልረባ ዕቃ አስገብተው ለሥራ ሳያውሉት መርካቶ የሚሸጡ ስንቶች ናቸው፡፡ ‘ብቻ ሆድ ይፍጀው’ ነው ‘ቤት ይቁጠረው’ የሚባለው፡፡ ይህን በመረጃ ለማስደገፍ ባልችልም እንዲሁ ግን ይታወቃል፡፡ ወይም ቀረጥ መቀነስ ካልቻለ መንግስት እራሱ ጣልቃ ገብቶ በተመጣጣኝ ዋጋ ከአቅራቢዎች ጋር ተስማምቶ የሚያስመጣበትን አሰራር ቢቀይስ ይሻላል፡፡ ይህም ካልተቻለ ደግሞ ልክ ቶርች ላይት አፕሊኬሽን ያላቸውን ሞባይሎች አገር ውስጥ መገጣጠም እንደተጀመረው ለትላልቅ ዓለም አቀፍ ኩባንያዎች ፈቃድ ሰጥቶ ሀገር ውስጥ እንዲሰሩ ማድረግ ጥሩ አማራጭ ነው፡፡
ከላይ ከተጠቀሱት አማራጮቹ የማንጠቀም ከሆነ ግን ወደፊታችን ምን እንደሚሆን አይታወቅም፡፡ ከቴክኖሎጂ ጋር አብረን መራመድ ብንችል ጥሩ ነው፡፡ በሀገራችን የሚቀረፁ ፊልሞችን ጥራት ብንመለከት እንኳን በ20ኛው ክፍለ ዘመን የተቀረፁ የቻርሊ ቻፕሊን ፊልሞችን እንኳን አያክሉም፡፡ ይህም የሚያመለክተው የሚቀርፁበት ካሜራ ልክ በባለ 2 ሜጋ ፒክስል ሞባይላችን እንደምንቀርጽበት አይነት ነው ማለት ነው፡፡ በአሁኑ ሰዓት HD (High Definition) የሚባሉ ካሜራዎችን ነው ዓለም ሁሉ የሚጠቀመው፡፡ እስካሁን ‘ጤዛ’ የተሰኘው የፕሮፌሰር ኃይለገሪማ ፊልም ብቻ ነው ጥርት ብሎ መስጦኝ ያዬሁት፡፡ ፊልም እኮ ታሪካዊ ፍሰቱ ብቻ አይደለም የሚመስጠው፤ አቀራረፁም ጭምር ነው፡፡  
ለማንኛውም ይህን ሁሉ የምቀባጥረው ስለፊልም ምንነት ለመናገር አይደለም፡፡ ወደ ዋናው ቁም ነገሬ ስገባ ሀገሪቷ ከቴክኖሎጂ ፈጠራዎች ተጠቅማ በፍጥነት ማደግ እንድትችል የቴክኖሎጂ ግብዓቶች ያስፈልጓታል፡፡ ከድንጋይ ተጠርቦ፣ ከእንጨት ተቀጣጥሎ የሚሰራበት የድንጋይ ዘመን ላይ አይደለም ያለነው፡፡ እነዚህ ፈጠራዎች የአኗኗር ዘይቤያችንን በመጠኑ ቢያሻሽሉትም ሙሉ በሙሉና ዘላቂ በሆነ መልኩ አይቀይሩትም፡፡ ዓለም እኮ ቆሞ አይጠብቀንም፡፡ እኛ ደግሞ በ2020 መካከለኛ ገቢ ካላቸው ሃገራት ተርታ አገራችንን እናሰልፋለን ብለን የምናወራው እኮ መቼም በሩጫና በእግር ኳስ አይደለም፡፡ ይልቁንም የህብረተሰቡን የኑሮ ደረጃ ፈርጀ-ሰፊ በሆነ መልኩ ለማሳደግ ነው፡፡
እናም አኔ የምለው አንድ በሉ ነው፡፡ ሌላማ ምንስ ልናገር፡፡ ይህ የኔ ድምፅ ብቻ አይደለም፡፡ ይልቁንም በኮምፒዩተር እጥረትና ናፍቆት የሚቃጠሉ የኔ ብጤዎችም ጭምር እንጂ፡፡

የመዲናችን ስብሰባዎች ብሶት


አዲስ አበባ፤ የውጭ እንግዶች መቀበያ፤ በእርግጥ እንግዶችን ማስተናገድ ባህላችን ቢሆንም፤ አንዳንዴ ግን ከገደብ ያልፋል፡፡ ይህን ለማለት ያበቃኝ ምን መሰላችሁ፡፡ ሁልጊዜ የአፍሪካ ህብረት ስብሰባ፣ የተለያዩ ሀገራት መሪዎች ስብሰባ፣ የሚኒስትሮች ስብሰባ፣ … ስብሰባ፣ በአጠቃላይ የጠቃሚ ሰዎች (VIP) ስብሰባ ሲኖር፤ በሚያጋጥመው የመንገድ መዘጋጋት ምክንያት በሃገሮው ሰዎች ላይ ይህ ነው የማይባል የጊዜና የኢኮኖሚ ቀውስ ያስከትላል፡፡ ታክሲ ለማግኘት አበሳ፣ ከተገኘ በኋላም ቀስ እያለ እየተንፏቀቀ በታሰበው ጊዜ ለመድረስ አይቻልም፡፡ ይህንን የማይረዱ ሰዎች አሉ፡፡ የቢሮ አለቃዎች አርፍደህ ስትገባ በአፍሪካ ህብረት ስብሰባ ምክንያት ነው ብትላቸው አይሰሙህም፡፡ እንዲያውም ይባስ ብሎ ከወር ደሞዝህ ይቆረጣል፡፡ ከዚህ አንፃር የአፍሪካ ህብረት መሪዎች የደሞዛችን ፀር ናቸው ማለት ይቻላል፡፡ ተማሪ ከሆንክና የፈተና ጊዜ ከሆነ፤ ሰዓት አሳልፈሃል ተብሎ ፈተና መቀመጥ አይችልም፡፡ ከዚህ ጋር ተያይዞ የትምህርት ፀር ስብሰባ ሆነ ማለት ነው፡፡ መች ይሄ ብቻ ለምሳሌ የነፍስ አድን ጥሪ የደረሰው የኔ ብጤ ባተሌ በታሰበው ጊዜ ደርሶ ቤተሰቡን ለማሳከም ጉዞ ቢጀምር የሚደርሰው ለቀብሩ ነው ማለት ነው፡፡
ከዚህ በተጨማሪም ፀሃፊው እንዳለው ስብሰባዎች ሲካሄዱ ብቻ የሚከፈቱ የቦሌ፣ የሜክሲኮና ሌሎች የማላውቃቸው በጣት የሚቆጠሩ ፋውንቴኖች አሉ፡፡ ይህም የሆነው ለውጭ ሰው ስለምናጎበድድ ነው እንጅ መቼም የውሃው ቁልፍ መሪዎቹ ኪስ ውስጥ ስለሚቀመጥ አይደለም፡፡ ያገሬ ሰው ፋውንቴን ማየት አያዝናናውም ወይ? እንዲያውም አብዛኛው ሰው እግረኛ ስለሆነ ከኔ ጀምሮ ማለቴ ነው፡፡ መቼም ፋውንቴን ሲመለከት ዘሎ ገብቶ ሻወር ልውሰድ የሚል እንደማይኖር ሁላችንም እናውቀዋለን፡፡ ምክንያቱስ የሀገሬ ሰው ለባህሉና ለወጉ ነው የሚቆመው፤ ማነው በአደባባይ ልብሱን አውልቆ ሻወር የሚወስደው፤ ይልቅስ ልብሱን አውልቆ ሽንቱን መሽናት ነው የሚቀናው፡፡ ይህንም ለማፅዳት ቢሆን ፋውንቴን ጠቃሚ ነው፡፡ መቼም ሃገራችን በውሃ እጦት አትታማም፡፡ አባይ አለ፤ አዋሽ አለ በየቦታው እየተጠማዘዘ እያጠጣ ጥም የሚቆርጥ፤ ኦሞ አለ፤ ባህርስ ብንል፤ ሃይቅስ ብንል፡፡ በእውነት በእውነት ምን የሌለን ነገር አለ፤ የሌለው ውቅያኖስ ብቻ እኮ ነው፡፡ እንዲያውም ሀገሪቷ ዝም ብላ በፀጋ የተሞላች እኮ ናት፡፡ እንዲያውም ኢትዮጵያ ቅፅል ስሟ እኮ የምስራቅ አፍሪካ የውሃ ማማ ነው የምትባለው፡፡ ታዲያ ምን ያደርጋል አለን እያልን ከማውራት ውጭ ስንጠቀምበት አይታይ፡፡
ለማንኛውም ስለውሃ አብዝቼ መናገሬ እያለን እንደሌለን ለምን እንሆናለን፤ ለኛ ያልፈሰሰ ፋውንቴን የውጭ ባዕድ ሀገር ሰዎች ሲመጡ ብቻ ለምን ይከፈታል ለማለት ያህል ነው፡፡ ለነገሩማ እኛ ኢትዮጵያውያን ስንባል በአዘቦት ቀን ሽሮ ስንከተክት እየከረምን የበዓል ቀን ሲመጣ አይደል ስጋን ጨምሮ ጥሩ ጥሩ ነገር የምንበላው፤ ከዚህስ ተያይዞ አይደለ ወይ የሽንኩርት፣ የቲማቲም፣ የቃሪያ፣ እና ወዘተ… ዋጋ የሚጨምረው፡፡ ይቅርታ የጠቀስኳቸው ምሳሌያዊ ምርቶች እኔ የምጠቀምባቸው ናቸው እንጂ የሌላውን አላውቅም፡፡ ፋውንቴን የሚከፈተውና መንገድ የሚዘጋው ለውጭ ሀገር ሰዎች ከሆነ ሀገራችን ውስጥ ያሉ ስለሀገራችን ብዙ የሚያውቁ፣ የሚፅፉ፣ የተማሩ፣ ፕሮፌሰሮች፣ ዶክተሮች እንዲሁም በዚህች ዓለም ላይ ብዙ ዝና ያላቸው ሰዎች ከተማችንን ከመመላለስም አልፎ ይኖሩባታል እኮ፡፡ እንዲያውም መሪዎች መጥተው ቤተ-መንግስትን ብቻ ነው አተኩረው ማየት የሚፈልጉት፡፡ ምክንያቱም የቤተ-መንግስት አሰራር ጥበብን ከኢትዮጵያ ኮርጀው የራሳቸውን አፍርሰው ለመገንባት ስለሚፈልጉ፡፡
ለማንኛውም የዚህች ከተማ ጣጣ በዚህ ብቻ የሚያበቃ አይደለም፡፡ እንዲያውም የተባ አንደበተኛ አለመሆኔ ነው እንጅ ስለዚህ ጉድ ለመፃፍ ቀለም አይነጥፍም ነበር፡፡ የእኛ ሀገር መሪዎች አሜሪካን ሀገር ቢሄዱ እንዴት ተብሎ ነው መንገድ የሚዘጋው፡፡ እንዲያውም ሴኩሪቲ ራሱ የሚመደብ አይመስለኝም፤ ግን አሜሪካ ሄጄ ስለማላውቅ ግምቴ ሊሳሳት ይችላል፡፡ የእኛ ሀገር ሰው ምንም ተንኮል አይሰራም፡፡ ለዚህም ማሳያው የሻእቢያና የአልሸባብ ሽብር ሳይፈጠር እንዲደረስበት የሚያደርገው ህዝቡ ነው፡፡ እንግዲያማ የሀገራችን ደህንነት በየትኛው መሳሪያ ተጠቅሞ ነው እንደዚህ የተቀነባበረ ዘመቻ ላይ ሊደርስበት የሚችለው፡፡ እንዲያውም አንዳንዴ የውጭ መሪዎች ገና ከአገራቸው ለአውሮፕላን ቡክ ሳያደርጉ ጀምሮ መንገዱ ክፍት ይደረግላቸዋል፤ ለእኛ ግን ተዘጋግቶ ማለት ነው፡፡ ግን እኮ መንገዱ ለኛም ክፍት ቢደረግ እነሱን ከፊት አድርገን እኛ ደግሞ ከኋላ ሆነን እያጨበጨብን እስ ቤተ-መንግስት እንሸኛቸው ነበር፡፡ ነገር ግን ብዙዎቹ የአፍሪካ መሪዎች በራሳቸው ስለማይተማመኑና በሚስታቸውም ስለማይታመኑ መክተሚያቸው አዲስ አበባን በንቃት ይከትሙባታል፡፡
በአጠቃላይ የሰው ወርቅ አያደምቅ ቢያደምቅም ለሞኝ ሰው ነው፤ ልክ መቼ ነው? የኢትዮጵያ ንግድ ባንክን ባሌስትራውን ወርቅ ቀብተው እንዳታለሉት ማለት ነው፡፡ ብለን እንጨርሰውና ስብሰባ ቢቀነስ ጥሩ ነው፤ ስብሰባ ቢኖርም ህብረተሰቡን በማይጎዳ መልኩ ቢሆን ጥሩ ነው፡፡ ለማንኛውም ይህ ሁሉ እሮሮ ሰሚ የሚያገኝ ከሆነ እሰየው፤ የማያገኝም ከሆነ እንዲያ እንደ ብሶት ይቀመጥና የወደፊታችንን እንዲያሳምረው ፀሎትና ዱዓ ማድረግ ሳይሻል አይቀርም፡፡

Ethiopian Overlooked and Underutilized Sector - Agriculture

Agriculture is the prominent sector of Ethiopia which millions of lives depend on for centuries. The share still stands high compared ...