Wednesday, March 19, 2014

ከ‹‹እንጃ›› በስተጀርባ

ሪፖርተር ጋዜጣ ላይ ደመቀ ከበደ የተሰኘ ገጣሚ ያቀረባት ግጥም ስለመሰጠችኝ ላካፍላችሁ ወደድኩ፡፡

==========

እኒያ የኔ ሰዎች

ከወንዝ ወዲያ ማዶ - በሩቅ የማያቸው

‹‹አትመጡም ወይ›› ብዬ - ለምጠይቃቸው

ከአፍ የሚወጣቸው

አንድ ነው ቃላቸው

‹‹እንጃ›› ነው መልሳቸው፤

እኒህም የኔዎች

አጠገቤ ያሉ - ሰርክ የማገኛቸው

ያልገባኝን ጉዳይ - ሁሌ ሳዋያቸው

ምንም ሳይዛነፍ - ‹‹እንጃ›› ነው መልሳቸው፤

‹‹ ከ‹እንጃ› ምሶሶና - ከ‹እንጃ› ባላ፣ ማገር

በ‹እንጃ› ባይ አናፂ - በታነፀች አገር

ከ‹እንጃ› ማለት በቀር

ለጥያቄ ሁሉ - ምላሽም አልነበር?››

ብየ እጠይቃለሁ

ብየ እጨነቃለሁ

ከጥያቄ ጋን ውስጥ - ጥያቄ እጠልቃለሁ፤

የምሬን እኮ ነው፤

‹‹ከ‹እንጃ› ባይ አገሬ

ከ‹እንጃ› የተሻለ - የአገር ምላሽ ባገኝ

‹ለምን?› አስረግዞ - ‹ለምን?› የወለደው - የሚያንገበግበኝ

ምላሽ ያጣሁለት - ጥያቄ ነበረኝ፤››

ብዬ እተክዛለሁ

ከጥያቄዬ ላይ - ጥያቄ እመዛለሁ፤

‹‹ማንን ነው ማዋየው - ወይ የማማክረው

የልቤ ጥያቄ - ልቤን ተረተረው፤››

እያልኩ አስባለሁ - ድንገት እነጉዳለሁ

ከጥያቄዬ ጋር - እወጣ እወርዳለሁ፤

ቢጨንቀኝ ጊዜ እንጂ፤

በ‹‹እንጃ›› አገር ተፈጥሮ - በ‹‹እንጃ›› ምላሽ አድጎ - ‹‹እንጃ›› ሲል ለኖረ

ከ‹‹እንጃ›› ማለት በቀር - ከ‹‹እንጃ›› የተሻለ - መልስም አልነበረ፤

ሀቅ ይኸውላችሁ፤

በዚች አገሬና - በዚች አገራችሁ

‹‹ምን ይበጀን ይሆን›› - ለሚል ጥያቄዬ - ለሚል ጥያቄያችሁ

‹‹እንጃ›› ነው ምላሹ - ‹‹እንጃልህ፣እንጃልሽ›› - ወይም ‹‹እንጃላችሁ››፡፡

© ደመቀ ከበደ

No comments:

Post a Comment

Ethiopian Overlooked and Underutilized Sector - Agriculture

Agriculture is the prominent sector of Ethiopia which millions of lives depend on for centuries. The share still stands high compared ...